
ዜና ሊቃነ ጳጳሳት !!
~★★~
• ይሄ እኔ ያለኝ መረጃ ነው። መፍትሄው እውነት መነጋገር ነው። አርነት የሚያወጣው እውነት መናገር ነው። ነጭ ነጯን መናገር እንጂ ዙሪያ ጥምጥም አያስፈልግም ባይ ነኝ።
ETHIOPIA | ~ ብፁዕ አቡነ መቃርዮስና ብፁዕ አቡነ ሩፋኤል።
•••
ብፁዕ አቡነ መቃርዮስ ፥
“ … የሶማሌ ሃገረ ስብከት ሊቀጳጳስ የነበሩት ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ በሶማሌ ክልል ተፈጥሮ የነበረውን የአሸባሪዎች ጥቃት ተከትሎ ወደ ሃገረ ስብከቱ ለመመለስ ባለመፍቀዳቸውና በመፍራታቸው ምክንያት ወደ ሶማሌ ሃገረ ስብከት የሚሄድ ሊቀጳጳስ በጠፋ ጊዜ የካናዳ ሀገረ ስብከታቸውን ትተው በፈቃደኝነት እሳት ውስጥ የገቡትና ኋላም የሐረሩ ሊቀጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሰላማም በህክምና ምክንያት ምሥራቅ ሀረርጌን ማስተዳደር ባልቻሉ ጊዜ ፥ ሱማሌንም ሀረርጌንም ደርበው፣ በየመቃብር ቤቱ ተኝተው እያደሩ።ገጠር ድረስ በመጓዝ በህይወት ዘመናቸው ጳጳስ አይተው የማያውቁ ምእመናንና ካህናትን በመጎብኘት፣ ከመንግሥት ባለሥልጣናትም ጋር ፊት ለፊት ተጋፍጠው የቤተ ክርስቲያንን መደፈር በጽኑ ተቃውመው፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በምሥራቅ ኢትዮጵያ ቀና እንድትል ያደረጉ አባት ናቸው ብፁዕ አቡነ መቃርዮስ።
•••
ብፁዕነታቸው በዚህ አስቸጋሪ ወቅት ነው በድንገት በገጠማቸው ህመም ምክንያት በሀገረ እስራኤል በሕክምና ሲረዱ ቆይተው ከትናንት ወዲያ በመጠኑ ተሽሏቸው ወደ ሀገር ቤት የተመለሱት። ከብፁዕነታቸው ጋር ተደዋውለን እንደተነጋገርነውም አሁን ላይ በመጠኑም ቢሆን ተሽሎኛል፣ ደግሞም የሚመጣውን መከራም ከህዝቤ ጋር ብቀበል ይሻለኛል ዘመዴ ነበር ያሉኝ። ብፁዕነታቸው አሁን አዲስ አበባ ናቸው።
•••
ብጹዕ አቡነ ሩፋኤል ፦
“ … በብዙ ክርክርና ውዝግብ የተሾሙ አባታችንም ጓደኛችን ናቸው። በቀደመው የህወሓት ዘመን በጋምቤላ ለሚኖሩ የህወሓት ባለሃብቶች ጥቅም ሲባል የጋምቤላ ክልል መንግሥት ለሲኖዶሱ ደብዳቤ ጽፎ በግድ ሲመተ ጵጵስናውን እንዲቀበሉ የተደተጉም አባት ናቸው። በጋምቤላም፣ በደቡብ ሱዳንና አሁን ደግሞ በምዕራብ ኢትዮጵያ አሶሳን ደርበው እንዲይዙም የተደረጉ አባት ናቸው።
•••
አባ ተክሌ ይፈጥናሉ። ይሄ ፍጥነታቸው ከአረጋዊያኑ ሊቃነጳጳሳት ጭምር ተግሳጽና ሃዘንም ይደርሳቸው ነበር። ሲበዛም የዋሕም ናቸው። እሳቸውን ተጠግተው ጥቅም ማጋበስ የሚፈልጉም የትዬለሌ ናቸው። በተለይ ምድረ ተሃድሶ እንደ ዝንብ ነው የሚወራቸው። ጎንደር ተወልደው አዲስ አበባ ሰባራ ባቡር አድገው ኋላም መቱ ኢሊባቦር ያደጉት ብፁዕነታቸው ለውጡን ተከትሎ ሥልጣን ላይ ያለው መንግሥት ኦሮሞ ነው በሚል እሳቤ ለቅዱስ ፓትርያርኩ ደብዳቤ በመጻፍ ለውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጭምር ዐማራ የተደረግኩት በስህተት ነው ኦሮሞ የሚል የዘር መታወቂያ እንዲሰጠኝ ስል በትህትና አመለክታለሁ በማለት ለኦሮሞ ያላቸውን ፍቅር በአደባባይ የገለፁም ምስኪን አባት ናቸው።
•••
ታዲያ አሁን እኚሁ ሊቀጳጳስ ባመኑት የኦሮሞ መንግሥትና፣ በፈቃደኝነት በደብዳቤ ጽፈው ኦሮሞነትን የተቀበሉት የኦሮሞ መንግሥት ህዝብ አደጋ ላይ ጥሏቸው ተገኝተዋል። ቄሮና የኦሮሚያ ፖሊስ ነን የሚሉ አካላት ( አንዳንዶች ሽፍቶች ናቸው ይላሉ) ሊቀጳጳሱን በጋራ አደጋ አድርሰውባቸው አሁን ሊቀጳጳሱ ሆስፒታል ተኝተዋል ተብሏል።
•••
ነገሩ እንዲህ ነው። አቡነ ሩፋኤል ከአዲስ አበባ ተነሥተው ከሹፌራቸው ጋር ወደ አሶሳ ሀገረ ስብከታቸው ጉዞ ይጀምራሉ። [ ይሄን ጉዞ የአሶሳ ምእመናን ቢቃወሙትም፣ ወደ ሀገረ ስብከታችን ድርሽ እንዳይሉብን ብለው በአካልም፣ በስልክም፣ በደብዳቤም እንዳሳሰቧቸው ተነግሯል] ሆኖም ሊቀጳጳሱ ጉዞ ወደ አሶሳ ቀጥለዋል። በጉዞአቸውም ላይ እግረ መንገዳቸውን 900ሺ ብርም በሻንጣ ይዘዋል። ጉዞው ቀጠለ፥ ቀጠለና ምእራብ ወለጋ አባ ሴና በተባለ ቦታ ላይ እንደደረሱ፣ የተደራጁ ቄሮዎች እና ፖሊሶች[ ሽፍቶችም የሚሉ አሉ] ሊቀጳጳሱን አሳፍራ ወደ ደምቢዶሎ በመገስገስ ላይ ያለችዋን መኪና ያስቆማሉ። “ ውረድ? አልውረድም። ማነህ? ምንድነህ መባባል ተጀመረ። ጭቅጭቅ ይፈጠራል። ቄሮና ሽፍታው መኪናዋን መፈተሽ ይጀምራሉ። ብር በሻንጣ ያገኛሉ። ጥያቄና መልስ ተጀመረ። የት ነው? ይሄን ያህል ብር ይዘህ የምትሄደው? አይመለከታችሁም። በመሃል ጭቅጭቁ እየከረረ መጣ። ይሄን ጊዜ የአቡኑ ሹፌር የማይገባ እርምጃ ወሰደ። ክላሽ ከመኪናው አውጥቶ ወደ ላይ ተኮሰ። ይሄን ጊዜ ድብልቅልቁ ወጣ። ነገር ተበላሸ።
•••
ታጣቂዎቹ በያዙት ዱላ ሊቀጳጳሱን ብፁዕ አቡነ ሩፋኤልን እግራቸው ላይ ደጋግመው ቀጠቀጧቸው። ሊቀጳጳሱ ወደቁ። ተኩሱን የሰማ ህዝብ ተሰበሰበ። መከላከያም ደረሰ። ጳጳሱን ወደ ህክምና ሹፌሩንም ያልተፈቀደ ህገወጥ የጦር መሣሪያ በመያዝ በሚል ወደ ካምፕ ወሰዱት። አሁን ሊቀጳጳሱ ብፁዕ አቡነ ሩፋኤል እዚያው ምዕራብ ወለጋ በአንድ የግል ህክምና ተቋም በመታከም ላይ ይገኛሉ።
•••
ሾፌሩ መሣሪያው የእኔ አይደለም በማለቱ ለጊዜው ተለቋል። የሊቀጳጳሱ መኪና ተጎድታለች። ሊቀጳጳሱ በደረሰባቸው የዱላ ድብደባ ምክንያት በህክምና ላይ ናቸው። መከላከያ ደርሶ የተዘረፈውን 900 ብር ለማስመለስ ጥረት ቢያደርግም ብሩን የያዘው አካል የብሩን ምንጭ ሳናውቅ፣ ብሩ ለምን ጉዳይ በዚህ መልኩ እንደሚሄድ ሳንረዳ አንለቅም ብሏል። እኔ ያለኝ መረጃ ይሄው ነው። የሌላውን አላውቅም። አከተመ።
•••
ጠረጋው ግን ከላይ ነው የሚጀምረው የተባለውን አውቃለሁ። ከላይ ከቤተ ክህነቱ። ከላይ ነው የሚጀምረው። እንደ መጽሐፉ ቃል በትህትና የማይኖሩ ሁሉ እገሌ ወእገሌ ሳይሉ ይጠረጋሉ። ይጋለጣሉ። ምንም መሸፋፈን አያስፈልግም። ሙዳየ ምጽዋቱን የዘረገፉ፣ ታቦቱን ያቀለሉ፣ የሸጡ፣ ቤተ ክርስቲያንን ያራቆቱ፣ ያስለቀሱ፣ ለመንጋው የማይራሩ ጨካኞች በሙሉ ይጠረጋሉ። ጅራፉ ከቤተ መቅደሱ ነው የሚጀምረው። እስቲ አሁን እናየለን። በተዘረፈ የሙዳየ ምጽዋት ገንዘብ በሠራኸው ቤት ተንደላቀህ ትኖር እንደሁ እናያለን። በባንካችን ያጠራቀምነው የቤተ ክርስቲያን ገንዘብ ያድነን እንደሁ እናያለን። ለጳጳስ መስቀል እንጂ ክላሽ ምን ያደርግለታል?
•••
ሻሎም ! ሰላም !
ዘመድኩን በቀለ ነኝ።
መጋቢት 9/2012 ዓም።
ከራየን ወንዝ ማዶ።





